09/12/2024
የኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስትና የኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት መካከል የተደረሰው የሠላም ስምምነት በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምና ልማት ለማረጋገጥ የጎላ ሚና ያለው ነው ሲሉ የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ሳይንስ መምህራን ተናገሩ።
ሌሎች ታጣቂ ሀይሎችም ከጠመንጃ ይልቅ የሰለጠነ አማራጭን ሊከተሉ እንደሚገባ ምሁራኑ ጠቁመዋል።
ሆሳዕና፦ 30/03/2017 ዓ.ም (ሀድያ ቴሌቪዥን)
የኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት አመራር የነበሩት ሰኚ ነጋሳ ከኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ ጋር በቅርቡ የሰላም ስምምነት መፈራረማቸው ይታወቃል።
የስምምነቱን ፋይዳ በተመለከተ ለሀድያ ቴሌቪዥን አስተያየታቸውን የሰጡት በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ሳይንስ ትምህርት ክፍል መምህራን የሆኑት መምህር ጌታሁን አበራ እና መምህር ሙሉጌታ አስፋው፤ የሰለም ስምምነቱ ለሀገሪቱ ሰላም እና ልማት መረጋገጥ ያለው አስተዋጽኦ ከፍ ያለ መሆኑን ገልጸዋል።
በትምህርት ክፍሉ የሰላምና ግጭት አፈታት መምህር ጌታሁን አበራ የሰላም ስምምነቱ የሀገሪቱ ኢኮኖሚ እንዲረጋጋ፣ ሰዎች ከቦታ ወደ ቦታ ያለ ስጋት እንዲንቀሳቀሱ እንዲሁም የቀድሞ ታጠቂ ሀይሎች ለሀገራቸው ልማት የበኩላቸውን እንዲወጡ በር የሚከፍት ነው ብለዋል።
ስምምነቱ ሌሎች ታጠቂ ሀይሎችም የሰላም አማራጭን እንዲከተሉ በር የሚከፍት መሆኑንም መምህር ጌታሁን ጠቁመዋል።
ሰላም የሁሉም ነገር መሰረት ነው ያሉት መምህር ጌታሁን የክልሉ መንግስትና ታጣቂ ቡድኑ ለሰላም ቅድሚያ በመስጠታቸው ሊመሰገኑ ይገባልም ብለዋል።
ሰላም በአንድ ጀንበር አይገነባም ያሉት መምህር ጌታሁን ሁሉም አካል ሰላምን ሊንከባከብ እና ለሰላም ዘብ መቆም እንደሚገባም አንስተዋል።
በዩኒቨርሲቲው በተመሳሳይ የትምህርት ክፍል መምህር የሆኑት መምህር ሙሉጌታ አስፋው፤ የሰላም ስምምነቱ ለሀገር ሰላም እና ልማት ያለውን አስተዋጽኦ ከፍ ያለ ነው የሚለውን የባልደረባቸውን ሀሳብ አጠናክረዋል።
ኦሮሚያ ክልል የሀገሪቱ እምብርት ላይ የሚገኝ ክልል እንደመሆኑ በክልሉ ውስጥ የሚፈጠሩ የሰላም ችግሮች የሀገሪቱ ሰላምና መረጋጋት ላይ አሉታዊ ጫና የሚያሳድር መሆኑን ጠቁመዋል።
በመሆኑም በክልሉ መንግስትና በሰኚ ነጋሳ በሚመራ ታጣቂ ሀይል መካከል የተደረሰው የሰላም ስምምነት ለኦሮሚያ ክልል ነዋሪዎች ብቻ ሳይሆን ለመላው ኢትዮጵያዊያን እፎይታን የሚሰጥ መሆኑን ጠቁመዋል።
ሰላም የሁሉም ነገር ቁልፍ መሆኑን የጠቆሙት መምህር ሙሉጌታ፤ ሁለቱም ሀይሎች ችግሮችን በሰላም ለመፍታት የወሰኑት ውሳኔ ኢትዮጵያ የምታተርፍበት መሆኑን ጠቁመዋል።
በወንድማማቾች መካከል በሚደረግ ውጊያ የሚመለስ የፖለቲካ ጥያቄ የለም ያሉት መምህር ሙሉጌታ፤ ሁለቱ ሀይሎች አለመግባባትን በሰላም ለመፍታት መወሰናቸው ይበል የሚያሰኝ ነው ብለዋል።
ምሁራኑ እንደተናገሩት ሁለቱ አካላት ስምምነት ከመፈራረማቸው ባሻገር በስምምነቱ የተነሱ ሀሳቦችን ተግባራዊ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆን አለባቸው።
በመሳሪያ ጥያቄያቸውን ለማስመለስ ጥረት የሚያደርጉ ሌሎች ታጣቂ ሀይሎችም፤ የሰላም አማራጭን ሊከተሉ እንደሚገባ ምሁራኑ ጠቁመዋል።
live events
17/09/2024
22/01/2024
22/01/2024
19/01/2024
19/01/2024
17/01/2024
14/01/2024