15/05/2026
አስቶን ቪላ ሊቨርፑልን በማሸነፍ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀመጠ
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 7፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 37ኛ ሳምንት መርሐ ግብር አስቶን ቪላ ሊቨርፑልን 4 ለ 2 አሸንፏል።
ምሽት 4 ሰዓት ላይ በቪላ ፓርክ ስታዲየም ሊቨርፑልን ያስተናገደው አስቶን ቪላ ሮጀርስ፣ ዋትኪንስ (ሁለት) እና ማክጊን ባስቆጠሯቸው ግቦች ድል አድርጓል።
የሊቨርፑልን ግቦች ቫን ዳይክ ከመረብ አሳርፏል።
በዚህም አስቶን ቪላ ነጥቡን 62 በማድረስ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
ሊጉን አርሰናል በ79 ነጥብ እየመራ ሲሆን÷ ማንቼስተር ሲቲ በ77 ነጥብ ሁለተኛ፣ ማንቼስተር ዩናይትድ በ65 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል።
ሊቨርፑል በ59 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
15/05/2026
ባህርዳር ከተማ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተጋጣሚዎቻቸውን አሸነፉ
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 7፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በ32ኛ ሳምንት የሲቢኢ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ባህርዳር ከተማ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተጋጣሚዎቻቸውን አሸንፈዋል፡፡
በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ከድሬዳዋ ጋር የተጫወተው ባህርዳር ከተማ 2 ለ 0 አሸንፏል፡፡
የጣና ሞገዶቹን ግቦች ፍፁም ፍትሃለው እና አንተነህ ተፈራ አስቆጥረዋል፡፡
በተመሳሳይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ከሸገር ከተማ ጋር የተጫወተው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 2 ለ 1 አሸንፏል፡፡
አዲስ ግደይ እና ናትናኤል ዳንኤል ለንግድ ባንክ ግቦቹን ሲያስቆጥሩ፤ የሸገር ከተማን ብቸኛ ግብ ቢኒያም ፍቅሩ አስቆጥሯል፡፡
15/05/2026
መቐለ 70 እንደርታ እና ኢትዮጵያ መድን አቻ ተለያዩ
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 7፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በ32ኛ ሳምንት የሲቢኢ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ መርሐ ግብር መቐለ 70 እንደርታ እና ኢትዮጵያ መድን 1 አቻ ተለያይተዋል፡፡
ቀን 7 ሰዓት ላይ አዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አብዱል ጋንዩ ኢትዮጵያ መድንን መሪ ቢያደርግም ብርሃኑ አዳሙ የመቐለ 70 እንደርታን የአቻነት ግብ አስቆጥሯል፡፡
በተመሳሳይ ስታዲየም ቀን 10 ሰዓት ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሸገር ከተማ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ፡፡
በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ደግሞ ቀን 10 ሰዓት ላይ ድሬዳዋ ከተማ ከባህርዳር ከተማ ይገናኛሉ፡፡
15/05/2026
ማንቼስተር ዩናይትድ አሰልጣኝ ማይክል ካሪክን በቋሚነት ሊሾም ነው
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 7፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ማንቼስተር ዩናይትድ ጊዜያዊ አሰልጣኙን ማይክል ካሪክ በቋሚነት ለመሾም የሁለት ዓመት ውል ማቅረቡ ተነግሯል፡፡
ማንቼስተር ዩናይትድ በውድድር ዓመቱ አጋማሽ አሰልጣኝ ሩበን አሞሪምን በማሰናበት ማይክል ካሪክን በጊዜያዊነት መሾሙ ይታወሳል፡፡
ክለቡ በአሰልጣኝ ማይክል ካሪክ እየተመራ ካደረጋቸው 15 ጨዋታዎች በ10ሩ ሲያሸንፍ፥ ሦስቱን አቻ ተለያይቶ ሁለት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል፡፡
በዚህም ክለቡ የሻምፒየንስ ሊግ ተሳትፎ እንዲያረጋግጥ ማስቻሉን ተከትሎ እስከ ፈረንጆቹ 2028 በቋሚነት እንዲያሰለጥን ውል እንደቀረበለት ዘ አትሌቲክ ዘግቧል፡፡
ለተጨማሪ አንድ ዓመት በክለቡ የሚያቆይ አማራጭ መካተቱንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
15/05/2026
ብሩኖ ፈርናንዴዝ የዓመቱ ምርጥ ተጫዋች ተብሎ ተመረጠ
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 7፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ብሩኖ ፈርናንዴዝ የማንቼስተር ዩናይትድ የ2025/26 የውድድር ዘመን የዓመቱ ምርጥ ተጫዋች ተብሎ ተመርጧል፡፡
ብሩኖ ፈርናንዴዝ የማንቼስተር ዩናይትድ የዓመቱ ምርጥ ተጫዋች ሽልማትን ሲያሸንፍ ለአምስተኛ ጊዜ ነው፡፡
ብሩኖ ፈርናንዴዝ በውድድር ዓመቱ በሊጉ ባደረጋቸው 33 ጨዋታዎች 19 ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ አቀብሏል፡፡
በዚህም የ31 ዓመቱ ተጫዋች ለጎል የሚሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ በማቀበል በውድድር ዓመቱ ቀዳሚው ተጫዋች ነው፡፡
ብሩኖ ፈርናንዴዝ ትናንት ይፋ በተደረገው የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የዓመቱ ምርጥ ተጫዋች ዕጩ ዝርዝር ውስጥ መካተት የቻለ ሲሆን የእግር ኳስ ጸሀፊዎች ማህበር የዓመቱ ምርጥ ተጫዋች ተብሎ መመረጡ ይታወሳል፡፡
15/05/2026
ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ለአሸናፊነት የሚጠበቁበት የሴቶች 10ሺህ ሜትር ሩጫ
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 7፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በ24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና አራተኛ ቀን ውሎ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ለተጨማሪ ድል የሚጠበቁበት ውድድር ዛሬ ቀጥሎ ይደረጋል፡፡
ምሽት 2 ሰዓት ከ05 የሴቶች የ10 ሺህ ሜትር የፍጻሜ ውድድር የሚደረግ ሲሆን፥ በርቀቱ ታዳጊዋ ስምረት በርሄ እና አሰፉ አብርሃ ኢትዮጵያን ይውክላሉ።
አትሌቶቹ ቀደም ሲል በሻምፒዮናው የተመዘገበውን ድል ለማስቀጠል ከፍተኛ ዝግጅት ማድረጋቸውን ተናግረዋል፡፡
ከዚህ ውድድር አስቀድሞ ምሽት 1 ሰዓት ከ45 በሚደረገው የወንዶች የ110 ሜትር መሰናክል የማጣሪያ ውድድር አትሌት ጌታሁን ታደሰ ወደ ቀጣዩ ዙር ለማለፍ ብርቱ ፉክክር ያደርጋል።
ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው ባሳየችው ድንቅ ብቃት እስካሁን በድምሩ 7 ሜዳሊያዎችን በመሰብሰብ በደረጃ ሰንጠረዡ አናት ላይ ትገኛለች።
በወርቅነህ ጋሻሁን
15/05/2026
አስቶን ቪላ ከሊቨርፑል - የሻምፒየንስ ሊግ ተሳትፎን ለማረጋገጥ
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 7፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ዛሬ ምሽት አስቶን ቪላ ከሊቨርፑል የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል፡፡
በእኩል 59 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው በሊጉ 4ኛ እና 5ኛ ደረጃ ላይ የሚገኙት ሁለቱ ክለቦች ምሽት 4 ሰዓት ላይ በቪላ ፓርክ ይገናኛሉ፡፡
የቀጣይ ዓመት የሻምፒየንስ ሊግ ተሳትፏቸውን ለማረጋገጥ የምሽቱን ጨዋታ ማሸነፍ ለሁለቱም ክለቦች በቂ ነው፡፡
ሁለቱ ክለቦች በሊጉ እርስ በእርስ ካደረጓቸው ያለፉት አምስት ጨዋታዎች ሊቨርፑል ሦስቱን ሲያሸንፍ፥ በሁለቱ ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል፡፡
15/05/2026
የፕሪሚየር ሊጉ የወርቅ ዋንጫ ባለቤት...
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 7፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) አርሰናል በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ38 ጨዋታዎች ውድድር አንድም ጨዋታ ሳይሸነፍ የወርቅ ዋንጫ ባለቤት መሆን የቻለ ብቸኛ ክለብ ነው።
የሰሜን ለንደኑ ክለብ "ዘ ኢንቪንስብል" (የማይበገሩት) በመባል ይህን ደማቅ ታሪክ የጻፈው ከ22 ዓመታት በፊት ልክ በዛሬዋ ዕለት ነበር።
በወቅቱ በፈረንሳዊው አሰልጣኝ አርሴን ቬንገር የሚመሩት መድፈኞቹ በሊጉ እስከዛሬም ድረስ ለሌሎች ክለቦች ያልተቻለውን ይህን ስኬት በ2003/4 የውድድር ዓመት አሳክተውታል።
በውድድር ዓመቱ በሊጉ ካደረጓቸው 38 ጨዋታዎች በ26ቱ ድል አድርገው በ12ቱ አቻ የተለያዩ ሲሆን፥ 90 ነጥቦችን በመሰብሰብ ከተከታያቸው ቼልሲ በ11 ነጥብ ርቀው ሻምፒዮን ሆነዋል።
ከአርሰናል አስቀድሞ በፈረንጆቹ 1888/9 ምንም ጨዋታ ባለመሸነፍ "ዘ ኢንቪንስብል" የሚል ማዕረግ ያገኘው ፕሪስተን ኖርዝ ኢንድ ነበር።
ሆኖም በወቅቱ በሊጉ በአንድ የውድድር ዓመት 27 ጨዋታዎች ብቻ ይደረጉ ስለነበር በ38 ጨዋታዎች ውድድር ይህን ያሳካ ብቸኛ ክለብ አርሰናል ሆኖ በታሪክ ሰፍሯል።
አርሰናል በዚያ የውድድር ዓመት አራት ጨዋታዎች እየቀሩት አስቀድሞ የሊጉ ሻምፒዮን መሆኑን ያረጋገጠ ሲሆን፥ ያለመሸነፍ ጉዞው ሊገታ የተቃረበባቸው አጋጣሚዎች ነበሩ።
በተለይም ከማንቼስተር ዩናይትድ ጋር ያለ ግብ አቻ ሆነው 90 ደቂቃ ከተጠናቀቀ በኋላ በባከነ ደቂቃ የፍጹም ቅጣት ምት የተሰጠባቸው አጋጣሚ ይታወሳል።
ሆኖም የሩድ ቫን ኒስትሮይ የፍጹም ቅጣት ምት ኳስ በግቡ አግዳሚ ተመልሶ መድፈኞቹ በሽርፍራፊ ሰከንዶች ከመሸነፍ የተረፉበት አጋጣሚ አይዘነጋም።
በተመሳሳይ ከሊጉ ላለመውረድ በሚጫወተው ሌስተር ሲቲ 1 ለ ዐ ከመመራት ተነስተው 2 ለ 1 ያሸነፉበት የመጨረሻ ሳምንት መርሐ ግብር የወርቅ ዋንጫውን ሊያጡ የተቃረቡበት አጋጣሚ እንደነበር ይጠቀሳል።
ጀርመናዊው ግብ ጠባቂ የንስ ሌማን 21 ጊዜ መረቡን ሳያስደፍር መውጣት ችሏል።
ለዚህም በሶል ካምቤል እና ኮሎ ቱሬ የሚመራው የመድፈኞቹ የተከላካይ መስመር ሚና ከፍተኛ ነበር።
በ30 ግቦች የሊጉ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ በመሆን ያጠናቀቀው ቲየሪ ሄንሪ የፕሪሚየር ሊጉ ዓመቱ ምርጥ ተጫዋች በመባል የተሸለመበት ዓመት ነበር።
ከሄንሪ በተጨማሪ ዴኒስ ቤርካምፕ፣ አማካዩ ፓትሪክ ቪዬራ እና የግራ መስመር ተከላካዩ አሽሊ ኮል ከዚያ ወርቃማ ስብስብ ውስጥ የሚጠቀሱ ተጫዋቾች ናቸው።
በ2002/3 የውድድር ዓመት መገባደጃ የተጀመረውና እስከ 2004/5 የውድድር ዓመት የዘለቀው የመድፈኞቹ የ49 ጨዋታዎች ያለመሸነፍ ጉዞ በፈረንጆቹ ጥቅምት 2004 በማንቼስተር ዩናይትድ መገታቱ አይዘነጋም።
የሰሜን ለንደኑ ክለብ ከዚያ ታሪካዊ ድል በኋላ ያላገኘውን የፕሪሚየር ሊጉ ዋንጫ ከ22 ዓመታት በኋላ ለማጣጣም ከጫፍ ደርሷል።
አርሰናል ከሁለት አስርት ዓመታት የተሻገረውን የሊግ ዋንጫ ጥም ለመቁረጥ ከበርንሌይ እና ክሪስታል ፓላስ ጋር የሚያደርጋቸውን ሁለት የመጨረሻ ጨዋታዎች ማሸነፍ በቂው ነው።
በኃይለማርያም ተገኝ
15/05/2026
ለ3ኛ ተከታታይ የውድድር ዓመት የፈረንሳይ ሊግ ሻምፒዮን - አሰልጣኝ ሉዊስ ኤንሪኬ
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 7፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ስፔናዊው አሰልጣኝ ሉዊስ ኤንሪኬ ለተከታታይ 3ኛ የውድድር ዓመት ከፒኤስጂ ጋር የፈረንሳይ ሊግ ዋንጫን ማሸነፍ ችለዋል፡፡
በፈረንጆቹ 1970 ስፔን ውስጥ በዛሬው ዕለት የተወለዱት አሰልጣኝ ሉዊስ ኤንሪኬ የአሰልጣኝነት ስራቸውን የጀመሩት በባርሴሎና ቢ ቡድን ነው፡፡
ከባርሴሎና ቢ ቡድን በመቀጠል ሮማ እና ሴልታቪጎን ያሰለጠኑት አሰልጣኙ በፈረንጆቹ 2014 የባርሴሎና ዋናውን ቡድን ተረክበዋል፡፡
በካታላኑ ክለብ ባርሴሎና በነበራቸው የአሰልጣኝነት ቆይታ የአውሮፓ ሻምፒየንስ ሊግ፣ የስፔን ላሊጋ፣ የስፔን ሱፐር ካፕ፣ ኮፓ ዴል ሬይ፣ የዓለም ክለቦች ዋንጫ እና የአውሮፓ ሱፐር ካፕ ዋንጫዎችን አሳክተዋል፡፡
ከባርሴሎና ጋር ከተለያዩ በኋላ የስፔን ብሔራዊ ቡድንን ከፈረንጆቹ 2018 እስከ 2022 አሰልጥነው በ2023/24 ወደ ፈረንሳዩ ክለብ ፒኤስጂ አቅንተዋል፡፡
የፓሪሱን ክለብ በ2023/24 ከተረከቡ ወዲህ የዘንድሮን ጨምሮ ለተከታታይ ሦስት የውድድር ዓመታት የሊጉን ዋንጫ ማሳካት ችለዋል፡፡
ፒኤስጂ በታሪኩ 14ኛ የፈረንሳይ ሊግ ዋንጫውን ያሳካ ሲሆን÷ በኤንሪኬ እየተመራ ደግሞ ያለፉትን ሦስት ተከታታይ የውድድር ዓመት ሻምፒዮን ሆኗል፡፡
ፒኤስጂ በሀገር ውስጥ ውድድር ስኬታማ ቢሆንም በአውሮፓ መድረክ ግን ተፎካካሪ ለመሆን እና ዋንጫ ለማንሳት የኤንሪኬን ፓሪስ መድረስ ይፈልግ ነበር፡፡
ፒኤስጂ የአውሮፓ ሻምፒየንስ ሊግ ዋንጫን ለማሳካት ሊዮኔል ሜሲ፣ ኔይማር ጁኒየር እና ኪሊያን ምባፔ የመሳሳሉ ተጫዋቾችን ቢያጣምርም ማሳካት እንዳልቻለ ይታወቃል፡፡
ከስፔናዊው አሰልጣኝ ሉዊስ ኤንሪኬ ፓሪስ መድረስ በኋላ ግን የክለቡ የዘመናት ጥያቄ ባሳለፍነው የውድድር ዘመን ምላሽ ማግኘቱ ይታወሳል፡፡
አሰልጣኝ ሉዊስ ኤንሪኬ የፈረንሳዩን ክለብ የአውሮፓ ሻምፒየንስ ሊግ የዘመናት ሕልም መፍታት የቻሉ ሰው ናቸው፡፡
ፒኤስጂ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ የአውሮፓ ሻምፒየንስ ሊግ ዋንጫን በፈረንጆቹ 2024/25 የውድድር ዓመት ሲያሳካ አሰልጣኝ ሉዊስ ኤንሪኬ በክለቡ ያመጡት ለውጥ ቀላል የሚባል አይደለም፡፡
አሰልጣኙ በአንድ ተጫዋች ላይ ጥገኛ ያልሆነ እንደ ቡድን የሚጫወት ጠንካራ ስብስብ በመገንባት ክለቡን ለዚህ ታላቅ ክብር አብቅተዋል፡፡
አሰልጣኝ ሉዊስ ኤንሪኬ አሁን የፈረንሳዩን ክለብ ፒኤስጂን በአውሮፓ ሻምፒየንስ ሊግ መድረክ ለተከታታይ የውድድር ዓመት ለፍጻሜ ማድረስ ችለዋል፡፡
የአሰልጣኝ ኤንሪኬ ቡድን በዚህ የውድድር ዓመት በአውሮፓ ሻምፒየንስ ሊግ ተጋጣሚዎቹ ላይ 44 ግቦችን ያስቆጠረ ሲሆን÷ በዚህም በውድድር ዘመኑ በመድረኩ በርካታ ግቦችን በማስቆጠር ቀዳሚው ሆኗል።
ቡድኑ በዚህ የውድድር ዓመት በመድረኩ ባየርን ሙኒክ፣ ሊቨርፑል፣ ቼልሲ እና ባርሴሎናን የመሳሰሉ ቡድኖችን ማሸነፉ ይታወሳል፡፡
ፒኤስጂ በአሰልጣኝ ሉዊስ ኤንሪኬ እየተመራ ለተከታታይ የውድድር ዓመት የአውሮፓ ሻምፒየንስ ሊግ ዋንጫን ያሳካ ይሆን የሚለው የሚጠበቅ ሲሆን÷ በፍጻሜው ከአርሰናል ጋር ጨዋታውን ያደርጋል፡፡
የአውሮፓ ሻምፒየንስ ሊግ የፍጻሜ ጨዋታ ግንቦት 22 ቀን 2018 ዓ.ም በሀንጋሪ ቡዳፔስት ፑሽካሽ አሬና ስታዲየም ይደረጋል።
በወንድማገኝ ጸጋዬ
14/05/2026
ኢትዮጵያ በ3 ሺህ ሜትር መሰናክል የወርቅና ነሐስ ሜዳሊያ አገኘች
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 6፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በጋና አስተናጋጅነት እየተካሄደ በሚገኘው 24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ በወንዶች 3 ሺህ ሜትር መሰናክል የፍጻሜ ውድድር የወርቅና ነሐስ ሜዳሊያ አግኝታለች።
በከፍተኛ ፉክክር በተካሄደው በዚህ ውድድር አትሌት ገመቹ ጎዳና ቀዳሚ በመሆን የወርቅ ሜዳሊያውን ለሀገሩ አስገኝቷል።
ገመቹ በተለይም በመጨረሻዎቹ ሜትሮች ላይ የነበሩትን መሰናክሎች በብቃት በመሻገርና ፍጥነቱን በመጨመር በአንደኝነት ለማጠናቀቅ ችሏል።
በተመሳሳይ ውድድር ላይ የተሳተፈው አትሌት ሳሙኤል ፍሬው ሦስተኛ ደረጃን ይዞ በማጠናቀቅ ለኢትዮጵያ የነሐስ ሜዳሊያ አስገኝቷል።
ይህ ሜዳሊያ ለኢትዮጵያ በሻምፒዮናው የተገኘ ሦስተኛው የነሐስ ሜዳሊያ ሆኖ ተመዝግቧል።
14/05/2026
ኢትዮጵያ ሁለተኛውን የወርቅ ሜዳሊያ አገኘች
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 6፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በ24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ ሁለተኛውን የወርቅ ሜዳሊያ አገኘች።
በ800 ሜትር ሴቶች ፍፃሜ ውድድር አትሌት ምስጋና ኃይሉ በቀዳሚነት በማጠናቀቅ ነው ሁለተኛውን የወርቅ ሜዳሊያ ማግኘት የተቻለው።
በተመሳሳይ በሴቶች የከፍታ ዝላይ ፍፃሜ አትሌት በፀሎት አለማየሁ ሦስተኛ ደረጃን ይዛ በማጠናቀቅ ለኢትዮጵያ ሁለተኛው ነሐስ ሜዳሊያ አስገኝታለች።
ሌላኛዋ በውድድሩ የተሳተፈችው አትሌት ሳራ ኝግዎ ደግሞ አምስተኛ ደረጃ በመያዝ አጠናቅቃለች።
በወርቅነህ ጋሻሁን