06/04/2026
ጁን 4 - 2026 (ግንቦት 27/2018) - ሮም ጣልያን
የ2026 ዳይመንድ ሊግ አራተኛ መዳረሻ በሆነው የሮሙ ጎልደንጋላ ፒዬትሮ ሜኒአ የሴቶች 5000ሜ. ውድድር ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የመጀመሪያዎቹን ሰባት ደረጃዎች በመቆጣጠር ጨርሰዋል፡፡ ልቅና አምባው የግሏን ምርጥ ከአምስት ሰከንድ በላይ ባሻሻለችበት እና የወቅቱ የርቀቱ ፈጣን በሆነ 14:18.41 ሰዓት ስታሸንፍ አለሺኝ ባወቀ (14:18.54 PB) እና ፍሬወይኒ ሀይሉ (14:18.94 PB) ሁለተኛ እና ሶስተኛ ሆነው ጨርሰዋል፡፡
ውድድሩን ካጠናቀቁት አስራ ስምንት አትሌቶች አስራ ሁለቱ የግል ምርጥ ሰዓታቻውን ያሻሻሉበት ይህ ፉክክር የባህሬን እና ፈረንሳይ ብሔራዊ ክብረወሰኖች የተሰበሩበትም ነው፡፡
የውድድሩ አሸናፊ የሆነችው ልቅና አምባው ካስመዘገበችው ድል በኋላ ለውድድሩ አዘጋጆች በሰጠችው አስተያየት ‹‹በዳይመንድ ሊግ ውድድር ላይ የመጀመሪያ ድሌን በማስመዝገቤ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡ (የእጅ ሰዓቷን ተመልክታ) ኦ እንደዚህ አይነት ሰዓት እንደሮጥኩ አላውቅም ነበር፡፡ በስታድየም ውስጥ የነበሩት ተመልካቾች በጣም ጥሩ ናቸው፡፡ የሞራል ድጋፋቸውም ከፍተኛ ነበር፡፡ በጣም ጠንካራ ስራዎችን ሰርቻለሁ በአጨራረስ የፍጥነት ሩጫዬ ላይ ጭምር፡፡ ለግዜው አምስት ሺህ ሜትር መሮጤን እቀጥላለሁ ወደፊት ምናልባትም በአስር ሺህ ሜትርም እወዳደር ይሆናል›› ብላለች፡፡
በሮም ዳይመንድ ሊግ የዳይመንድ ሊጉ የነጥብ ፉክክር አካል ባልነበረው የሴቶች 1500ሜ. ውድድር የግሬት ብሪቴይኗ ጆርጂያ ሀንተር ቤል (3:58.63 SB) ስታሸንፍ ብቸኛዋ ኢትዮጵያዊት ተወዳዳሪ የነበረችው ሐረገወይን ካላዩ 4:03.43 በሆነ ሰዓት ዘጠነኛ ሆና ጨርሳለች፡፡
06/03/2026
ጁን 3/2026 (ግንቦት 26-2018) ቱርኩ - ፊንላንድ
የወርቅ ደረጃ ባለው እና የአለም አትሌቲክስ ኮንቲኔንታል ቱር አካል በሆነው የ2026 የፓቮ ኑርሚ ጨዋታዎች የሴቶች 3000ሜ. መሰናክል ውድድር ኢትዮያዊቷ አለምናት ዋለ 9፡16.18 በሆነ ሰዓት አሸናፊ ሆናለች፡፡
በሴቶች 1500 ሜትር ውድድር ላይ የተሳተፈችው ኢትዮያዊቷ ኬና ቱፋ 9፡16.18 በሆነ ሰዓት ዘጠነኛ ሆና ስትጨርስ በወንዶች 5000 ሜትር ውድድር ላይ የተፎካከረው ጌትነት ዋለ 13፡03.95 በሆነ ሰዓት አራተኛ ወጥቷል፡፡
ጌትነት አራተኛ በወጣበት የወንዶች 5000 ሜትር የመጀመሪያዎቹን ሶስት ደረጃዎች ይዘው ያጠናቀቁት ሶስቱም አትሌቶች - ሁለቱ ጀርመናውያን ፍሎሪያን ብሬመ (12፡56.80) እና ፍሬድሪክ ሩፐርት (12፡57.61) እንዲሁም የብሩንዲው ኤዢድ ንታካሩቲማና (12፡59.45) - የግል ምርጥ ሰዓታቸውን ያሻሻሉበትን ከ13 ደቂቃ በታች የሆነ ሰዓት አስመዝግበዋል፡፡
Paavo Nurmi Games
06/03/2026
ጁን 3/2026 (ግንቦት 26-2018) ቱርኩ - ፊንላንድ
የወርቅ ደረጃ ባለው እና የአለም አትሌቲክስ ኮንቲኔንታል ቱር አካል በሆነው የ2026 የፓቮ ኑርሚ ጨዋታዎች የወንዶች 3000ሜ. መሰናክል ውድድር ኢትዮያዊው አብርሀም ስሜ ሁለተኛ በመሆን አጠናቋል፡፡ ውድድሩን በአንደኛነት የጨረሰው ሞሮኳው ሞሐመድ ቲንዱፍ ነው፡፡
06/02/2026
የውድድሩ አዘጋጆች ይፋ ባደረጉት የተፎካካሪዎች ዝርዝር መሰረት 14 ኢትዮጵያውያን ሴት አትሌቶች ሐሙስ ጁን 4 ቀን 2026 (ግንቦት 27/2018) በሮም ጣልያን በሚካሄደው የሮም ዳይመንድ ሊግ ላይ ይወዳደራሉ። የሮም ዳይመንድ ሊግ (Golden Gala Pietro Mennea) የ2026 የዳይመንድ ሊግ አራተኛ መዳረሻ ነው፡፡
በሴቶች 1500ሜ.
ብርቄ ሀይሎም 3:53.22 PB
ወርቅነሽ መሰለ 3:57.00 PB
ሳሮን በርሔ 3:57.72 PB
በሴቶች 5000ሜ.
መዲና ኢሳ 14:16.54 PB
ፍሬወይኒ ሀይሉ 14:19.33 PB
ልቅና አምባው 14:24.21 PB
ሰናይት ጌታቸው 14:24.71 PB
አለሺኝ ባወቀ 14:27.33 PB
ሒሩት መሸሻ 14:29.29 PB
ፋንታዬ በላይነህ 14:30.90 PB
ማርታ አለማየሁ 14:32.84 PB
የኔዋ ንብረት 14:39.13 PB
የኔነሽ ሽመክት 14:48.02 PB
አልማዝ ባራኪ -
06/02/2026
የዓለም አትሌቲክስ ሶስት የአለም እና ሶስት የዓለም ከ20 ዓመት በታች በድምሩ ስድስት የዓለም ክብረወሰኖችን ማፅደቁን ዛሬ ጁን 1-2026 (ግንቦት 24-2018) ባወጣው መግለጫ (Press release) አሳውቋል፡፡ ከፀደቁት ስድስት የዓለም ክብረወሰኖች መካከል ሁለቱ የተመዘገቡትም በኢትዮጵያውያኑ አትሌቶች ዮሚፍ ቀጄልቻ እና ሳሮን በርሔ ስም ነው፡፡
ዮሚፍ ቀጄልቻ በፌብሩዋሪ 16 ቀን 2025 ዓ.ም. በስፔን ካስቴዮን ባስመዘገበው 26፡31 የሆነ ሰዓት የ10 ኪሎ ሜትር የዓለም ክብረወሰን ባለቤት ለመሆን በቅቷል፡፡ ዮሚፍ የክብረወሰኑ ባለቤት ለመሆን የበቃው ኬንያዊው ሮኔክስ ኪፕሩቶ በጃንዋሪ 2020 በቫሌንሲያ አስመዝግቦት ይዞት የቆየው 26፡24 ክብረወሰን ውጤት በፀረ-አበረታች ቅመሞች ህግ ጥሰት ምክንያት መሰረዙን ተከትሎ ነው።
ሳሮን በርሔ በሴቶች 1500 ሜትር የቤት ውስጥ ውድድር ፌብሩዋሪ 3-2026 በቼክ ሪፐብሊክ ኦስትራቫ ሁለተኛ ሆና ስታጠናቅቅ ያስመዘገበችው 4፡01.23 ሰዓት የዓለም ከ20 አመት በታች የርቀቱ ክብረወሰን ሆኖ ፀድቆላታል፡፡ ሳሮን ያሻሻለችው ክብረወሰን በኢትዮጵያዊቷ ለምለም ሀይሉ በ2020 ዓ.ም. በፈረንሳይ ሊዬቨ ተመዝግቦ የነበረው 4፡01.57 የሆነ ሰዓት ነው።
የዓለም አትሌቲክስ መግለጫ የሳሮን በርሔ ዕድሜ በመጪው ነሐሴ ወር በዩናይትድ ስቴትስ ኦፍ አሜሪካ ኦሬገን ውስጥ በሚካሄደው ከ20 ዓመት በታች የዓም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ለመሳተፍ ብቁ እንደሚደርጋትም ጨምሮ ገልጿል፡፡
06/01/2026
ዕሁድ ሜይ 31-2026 (ግንቦት 23-2018) ራባት-ሞሮኮ
በራባት ዳይመንድ ሊግ የዳይመንድ ሊጉ የነጥብ ፉክክር አካል ባልሆነው የሴቶች 1500 ሜትር ውድድር ኢትዮጵያውያኑ ፍሬወይኒ ሀይሉ እና ሐረገወይን ካላዩ በቅደም ተከተል አንደኛ እና ሁለተኛ ወጥተዋል፡፡
የሴቶች 1500m ውጤት:-
1. ፍሬወይኒ ሀይሉ 🇪🇹 3:58.25
2. ሐረገወይን ካላዩ 🇪🇹 3:59.28
3. አጋት ጉዬልሞ 🇫🇷 3:59.60
4. ፓትሪሺያ ሲልቫ 🇵🇹 4:00.40
5. ላውራ ሙዪር 🇬🇧 4:00.77
6. ሉሲያ ስታፎርድ 🇨🇦 4:00.83
7. ልቅና አምባው 🇪🇹 4:01.56
8. አስቴር አሬሪ 🇪🇹 4:01.70
12. ዮርዳኖስ ፀጋአብ 🇪🇹 4:03.99
16. ሳምራዊት ሙሉጌታ 🇪🇹 4:08.81
በዳይመንድ ሊጉ የወንዶች 3000 ሜትር መሰናል ፉክክር ሞሮኳዊው ሶፊያን ኤል ባካሊ የወቅቱ ፈጣን በሆነ 7:57.25 ሰዓት ሲያሸንፍ ኢትዮጵያዊው ሳሙኤል ፍሬው የግሉ የዓመቱ ምርጥ በሆነ 8:12.55 ሰዓት 12ኛ ሆኖ ጨርሷል፡፡
በራባት የወንዶች 1500 ሜትር ውድድር ላይ እንደሳሚተፍ ተገልፆ የነበረው ኢትዮጵያዊው ለሜቻ ግርማ ባልተገለፀ ምክንያት በውድድሩ ላይ አልተገኘም፡፡
05/31/2026
ዕሁድ ሜይ 31-2026 (ግንቦት 23-2018) ራባት-ሞሮኮ
በሲውዘርላንዳዊቷ ኦድሬ ቬሮ (1:56:56) አሸናፊነት በተጠናቀቀው የራባት ዳይመንድ ሊግ የሴቶች 800 ሜትር ውድድር ኢትዮጵያዊቷ ፅጌ ድጉማ (1:57:24) ሁለተኛ ወጥታለች።
ንግስት ጌታቸው 1:58:58 በሆነ ሰዓት 11ኛ ሆና ጨርሳለች።
05/31/2026
ኢትዮጵያዊው ሰለሞን ባረጋ በ2026 ግሬት ማቸስተር ራን የጎዳና ላይ የወንዶች 10 ኪ.ሜ. ፉክክር ያለፈው ዓመት አሸናፊነት ክብሩን ማስጠበቅ የቻለበትን ድል ተቀዳጅቷል፡፡
📸 Great Manchester Run
05/30/2026
የዋንዳ ዳይመንድ ሊግ ነገ እሁድ ሜይ 31-2026 (ግንቦት 23-2018) ብቸኛው የአፍሪካ መዳረሻው በሆነችው የሞሮኮዋ ራባት ከተማ በርካታ የኦሊምፒክ እና የአለም ሻምፒዮን አትቶችን በማሳተፍ ይቀጥላል። የ2026 ዓ.ም. ሶስተኛው ውድድር ላይ ከሚካሄዱት ውድድሮች አንዱ በሆነው የወንዶች 3000 ሜትር መሰናል ኢትዮጵያዊው ሳሙኤል ፍሬው ይሳተፋል፡፡ የርቀቱ የኦሊምፒክ እና የዓለም ሸምፒዮኑ ሶፊያን ኤል ባካሊም የዓመቱን የመጀመሪያ ውድድሩን በሀገሩ በሞሮኮ ዋና ከተማ ራባት በሚካሄደው በዚህ ውድድር ላይ የሚያደርግ ይሆናል።
በ2025ቱ የቶኪዮ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የወንዶች 3000ሜ. መሰናክል የወርቅ ሜዳሊያ ያሸነፈው ኒው ዚላንዳዊው ጆርዲ ቢሚሽ፣ የብር ሜዳልያ አሸናፊው ሞሮኳዊው ሶፊያን ኤል ባካሊ፣ የነሐስ ሜዳልያ ባለቤቱ ኬንያዊው ኤድሙንድ ሴረም፣ እና አራተኛ የወጣው ኢትዮጵያዊው ሳሙኤል ፍሬው የተካተቱበት ይህ ውድድር የራባት ዳይመንድ ሊግ ፕሮግራም የመዝጊያ ውድድር ነው፡፡
ሳሙኤል ፍሬው ባለፈው ዓመት በቻይና ሺያመን ዳይመንድ ሊግ ፉክክር ላይ ኤልባካሊን ቀድሞ በመግባት አሸናፊ መሆን መቻሉ ይታወሳል፡፡ ዘንድሮስ በራባት?...