08/06/2026
በዓለም ከ20 ዓመት በታች የአትሌቲክስ ሻምፒዮና የመክፈቻ ቀን የምሽት ፕሮግራም በተደረገው የወንዶች 5000 ሜትር የፍፃሜ ውድድር ኬንያውያኑ አትሌቶች ፍራንክሊን ኪቤት (13፡28.27) እና ኔሄሚያ ኪፕንጌኖ (13፡30.09) የወርቅ እና የብር ሜዳልያውን ሲያሸንፉ ኢትዮጵያዊው ዳምጠው ከበደ (13፡35.38 PB) የነሐስ ሜዳልያውን ወስዷል፡፡ ሁለቱ ኬንያውያ እና ሁለቱ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ሶስት ዙር ሲቀር ወደፊት ወጥተው ባደረጉት ፉክክር ኬንያውያኑ 600 ሜትር ሲቀር ኢትዮጵያውያኑን ተፎካካሪዎቻቸውን አስለቅቀው በመሄድ ድል አድርገዋል፡፡ በዚህ ውድድር ላይ ተሳታፊ የነበረው ሌላኛው ኢትዮጵያዊት ማማሩ ጓዴ (13፡44.41) አምስተኛ ሆኖ አጠናቋል፡፡
08/06/2026
በዓለም ከ20 ዓመት በታች የአትሌቲክስ ሻምፒዮና የመክፈቻ ቀን የምሽት ፕሮግራም በተደረገው የሴቶች 5000 ሜትር የፍፃሜ ውድድር ኡጋንዳዊቷ ቻሪቲ ቼሮፕ (15፡03.88) የወርቅ ሜዳልያውን ስትወስድ ሽቶ ጉሚ (15፡07.91) ለኢትዮጵያ የብር ሜዳልያ አስገኝታለች፡፡ በሶስቱ የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ኡጋንዳ፣ ኬንያ፣ እና ኢትዮጵያ አትሌቶች መካከል በነበረው ፉክክር ሶስቱም አንድ አንድ ሜዳልያ ሲያገኙ ኬንያ በጆይሊን ቼፕኬሞይ (15፡09.08 PB) አማካይነት የነሐስ ሜዳልያው ባለቤት ሆናለች፡፡ በዚህ ውድድር ላይ ተሳታፊ የነበረቸው ሌላኛዋ ኢትዮጵያዊት እመቤት ጥላሁን (15፡32.51) ስድስተኛ ሆና ጨርሳለች፡፡
08/06/2026
በዓለም ከ20 ዓመት በታች የአትሌቲክስ ሻምፒዮና የመክፈቻ ቀን የምሽት ፕሮግራም በሴቶች 3000 ሜትር መሰናክል የማጣሪያ ውድድር ላይ የተካፈሉት ኢትዮጵያውያኑ ወሰኔ አሰፋ እና አልማዝ ዮሐንስ ለፍፃሜው ውድድር አልፈዋል፡፡
በምድብ ሁለት የተወዳደረችው አልማዝ ዮሐንስ 9:42.45 በሆነ ሰዓት አንደኛ በመውጣት ስታልፍ ወሰኔ አሰፋ ከምድብ አንድ 9:56.36 በሆነ ሰዓት ሁለተኛ ወጥታ ነው ልፍፃሜው የበቃችው፡፡ በማጣሪያ ውድድሮቹ ላይ በተስተዋለው መሰረት በፍፃሜው ለሶስቱ ሜዳልያዎች አሸናፊነት የሚደረገው ትንቅንቅ በአራቱ አትሌቶች (በሁለት ኢትዮያውያን እና ሁለት ኬንያውያን) መካከል እንደሚሆን አያጠራጥርም፡፡
08/05/2026
በዓለም ከ20 ዓመት በታች የአትሌቲክስ ሻምፒዮና የሁለተኛ ቀን ፕሮግራም መሰረት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በሁለቱም ፆታዎች የ1500 ሜትር የማጣሪያ ውድድሮች ላይ ይሳተፋሉ፡፡
በሶስት ምድብ ተከፍሎ በሚካሄደው የወንዶች 1500 ሜትር ከየምድቡ የመጀመሪያዎቹን አምስት ደረጃዎች ይዘው የሚያጠናቅቁ አትሌቶች ለፍፃሜው የሚያልፉ ይሆናል፡፡ በማጣሪያው በምድብ አንድ የሚወዳደረው ደስታው ታዴ ብቸኛው የኢትዮጵያ ተወካይ ነው፡፡
ሐረገወይን ካላዩ (ምድብ ሁለት) እና ኤልሳቤት አማረ (ምድብ ሶስት) በሶስት ምድብ ተከፍሎ በሚካሄደው የሴቶች 1500 ሜትር ማጣሪያ ላይ የኢትዮጵያ ተሰላፊዎች ናቸው፡፡
08/05/2026
በዓለም ከ20 ዓመት በታች የአትሌቲክስ ሻምፒዮና ኬንያዊቷ ናንሲ ጄፕንጌቲች በሴቶች የ800 ሜትር የማጣሪያ ውድድር ከምድብ ሁለት ከሁሉም ምድቦች በፈጠነ 2፡01:25 የሆነ ሰዓት አሸናፊ ነበረች፡፡ ሆኖም ከመሮጫ መስመሯ ውጭ በመሮጧ ውጤቷ ውድቅ (Disqualify) ተደርጓል። ናንሲ ጄፕንጌቲች ሜዳሊያ ያሸንፋሉ ተብለው ከሚጠበቁት አትሌቶች መካከል አንዷ ነበረች።
At the World U20 Athletics Championships ( ), Kenya's Nancy Jepngetich won the second heat of the women's 800m with a time of 2:01.25, the fastest across all heats, but was disqualified for running out of her lane. She was one of the favourites to win a medal.
08/05/2026
በዓለም ከ20 ዓመት በታች የአትሌቲክስ ሻምፒዮና የመክፈቻ ቀን ጠዋት፣ ኢትዮጵያን ወክለው የተወዳደሩት ሀብታም ገበየሁ እና ደራርቱ ሽብሩ በአምስት ምድብ ተከፍሎ በተካሄደው የሴቶች የ800 ሜትር የማጣሪያ ውድድር ለግማሽ ፍጻሜው አልፈዋል።
በምድብ አራት የተወዳደረችው ሀብታም ገበየሁ 2:04.66 በሆነ ሰዓት አንደኛ በመውጣት ስታልፍ ደራርቱ ሽብሩ ከምድብ አንድ 2:10.28 በሆነ ሰዓት አምስተኛ ሆና አጠናቃ ግማሽ ፍፃሜውን ተቀላቅላለች፡፡
08/05/2026
በዓለም አትሌቲክስ ከ20 ዓመት በታች ሻምፒዮና የመጀመሪያ ቀን የጠዋት ውድድሮች ፕሮግራም በአምስት ምድብ ተከፍሎ በተካሄደው የወንዶች 800 ሜትር የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ኢትዮጵያን ወክለው የተወዳደሩት ሁለቱም አትሌቶች ለግማሽ ፍፃሜው አልፈዋል፡፡
ነጋሄ እያሱ ከምድብ አንድ 1:51.16 በሆነ ሰዓት አንደኛ በመውጣት ሲያልፍ የሮሳን ግርማ ግማሽ ፍፃሜውን የተቀላቀለው ከምድብ ሁለት የግሉን ምርጥ ሰዓት ባሻሻለበት 1:46.64 የሆነ ሰዓት አራተኛ ሆኖ አጠናቆ ነው፡፡
08/05/2026
በዓለም አትሌቲክስ ከ20 ዓመት በታች ሻምፒዮና የመጀመሪያ ቀን ውድድሮች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በሶስት የማጣሪያ እና ሁለት የፍፃሜ ውድድሮች ላይ ይሳተፋሉ፡፡
በሁለቱም ፆታዎች በአምስት ምድብ ተከፍሎ በሚካሄደው የ800 ሜትር የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ
በወንዶች
ነጋሄ እያሱ - ምድብ አንድ
የሮሳን ግርማ - ምድብ ሁለት
በሴቶች
ደራርቱ ሽብሩ - ምድብ አንድ
ሀብታም ገበየሁ - ምድብ አራት
በሁለት ምድብ ተከፍሎ በሚካሄደው የሴቶች 3000 ሜትር መሰናክል ማጣሪያ
ወሰኔ አሰፋ - ምድብ አንድ
አልማዝ ዮሐንስ - ምድብ ሁለት
የሁለቱም ፆታዎች የ5000 ሜትር የፍፃሜ ውድድርም በመጀመሪው ቀን የሚደረግ ሲሆን
በወንዶች
ማማሩ ጓዴ እና ዳምጠው ከበደ
በሴቶች
ሽቶ ጉሚ እና እመቤት ጥላሁን ኢትዮጵያን ወክለው ለሜዳልያ አሸናፊነት ሚፎካከሩ ይሆናል፡፡
ፎቶ ክሬዲት ሀገሬ ቴቪ- Hagerie TV
ውድድሩን ኢትዮጵያ ያላችሁ በሀገሬ ቲቪ በካናዳ የምትኖሩ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ አፍቃሪዎች ደግሞ በሲቢ ስፖርት መከታተል ትችላላችሁ
https://gem.cbc.ca/world-athletics-u20-championships-oregon-day-1-morning-session-37148?autoplay=1
08/05/2026
የዓለም አትሌቲክስ ከ20 ዓመት በታች ሻምፒዮና
የኢትዮጵያ አትሌቶች የመጀመሪያ ቀን ውድድሮች ፕሮግራም
World Athletics U20 Championships
Ethiopian athletes' day one competition program