EBC SPORT ኢቢሲ ስፖርት

EBC SPORT ኢቢሲ ስፖርት

Share

EBC Sport is one of Ethiopian Broadcasting Corporation social media focusing on Sports.

Photos from EBC SPORT ኢቢሲ ስፖርት's post 02/06/2026

ኤቨርተን ኢሊማን ንዲያዬን ለማቆየት እየታገለ ይገኛል
********************

ኤቨርተን አጥቂው ኢሊማን ንዲያዬ የቀረበለትን አዲስ የውል ማራዘሚያ ጥያቄ ውድቅ ማድረጉን ተከትሎ ተጫዋቹን በክለቡ የማቆየት ከባድ ፈተና ገጥሞታል።

​በክለቡ እና በተጫዋቹ ወኪሎች መካከል የሚደረገው ንግግር ከዓመቱ መጀመሪያ ጀምሮ እየተካሄደ ቢሆንም እስካሁን ድረስ ምንም ዓይነት ስምምነት ላይ መድረስ አልተቻለም።

ዘ አትሌቲክ ይዞት የወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው ለስምምነቱ መዘግየት አንዱና ዋነኛው ምክንያት በውሉ ላይ እንዲካተት የተጠየቀው የውል ማፍረሻ ክፍያ ሲሆን፣ ኤቨርተን በማንኛውም የወደፊት ዝውውር ላይ ሙሉ ቁጥጥር እንዲኖረው ይፈልጋል።

​በክረምቱ የተጫዋቾች የዝውውር መስኮት የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳታፊ የሆኑ ክለቦች፣ ተጫዋቹን ለማስፈረም ጥረት ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። ነገር ግን ኤቨርተን የ26 ዓመቱን ተጫዋች ለማቆየት ቆርጦ ተነስቷል።

ንዲያዬ በአሁኑ ውሉ ላይ አሁንም ሶስት ዓመት የሚቀረው ሲሆን፣ በክለቡ ውስጥ ካሉ እጅግ ውድ ተጫዋቾች አንዱ ተደርጎ ይወሰዳል።

​የቀድሞው የሼፊልድ ዩናይትድ እና የማርሴይ አጥቂ ባለፈው የውድድር ዘመን 6 የፕሪሚየር ሊግ ግቦችን አስቆጥሯል።

በዓለም ዋንጫው ላይ ለሴኔጋል ብሔራዊ ቡድን ድንቅ ብቃቱን የሚያሳይ ከሆነ ይበልጥ የብዙዎችን ትኩረትን ይስባል ተብሎ ይጠበቃል።

በእሱባለው ተሾመ

Photos from EBC SPORT ኢቢሲ ስፖርት's post 02/06/2026

የቱርክዬ ብሄራዊ ቡድን የዓለም ዋንጫ ስብስቡን ይፋ አድርጓል
***************

የቱርክዬ ብሔራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ቪንቼንዞ ሞንቴላ የዓለም ዋንጫ የመጨረሻ የ26 ተጫዋቾች ስብስባቸውን ይፋ አድርገዋል።

ስብስቡ በአውሮፓ ታዋቂ ሊጎች እና በቱርክዬ በአገር ውስጥ ክለቦች በሚጫወቱ ተጫዋቾች የተዋቀረ ነው።

የ21 ዓመቱ የሪያል ማድሪድ አማካይ አርዳ ጉለር፣ የማንቸስተር ዩናይትዱ ግብ ጠባቂ አልታይ ባይንድር፣ የብራይተኑ ተከላካይ ፈርዲ ካዲኦግሉ እንዲሁም የዩቬንቱሱ አማካይ ኬናን ዩልዲዝ በስብስቡ ውስጥ ከተካተቱ ታዋቂ ተጫዋቾች መካከል ናቸው።

ግብ ጠባቂው ሙሀመድ ሼንጌዘር፣ አራል ሺምሺር እና ደሚር ኤገ ቲክናዝ ባይካተቱም፤ በፊፋ ሕግ መሠረት ጉዳት ካጋጠመ ለመተካት እንዲቻል ወደ አሜሪካ አብረው ይጓዛሉ።

ቡድኑ ዛሬ ወደ ፍሎሪዳ፣ ፎርት ላውደርዴል የሚያቀና ሲሆን፤ ሰኔ 7 ቀን በኢንተር ማያሚ ስታዲየም ከቬንዙዌላ ጋር የመጨረሻ የዝግጅት የወዳጅነት ጨዋታውን ያደርጋል።

ከ24 ዓመት በኋላ ወደ ዓለም ዋንጫው የተመለሰችው ቱርክዬ በምድብ 4 ከአውስትራሊያ፣ ፓራጓይ እና ከአዘጋጇ አሜሪካ ጋር ተደልድላለች።

በአሜሪካ፣ ካናዳ እና ሜክሲኮ አስተናጋጅነት የሚካሄደው የ2026 ዓለም ዋንጫ ሰኔ 4 የሚጀምር ይሆናል።

በይበልጣል ሰውነት

Photos from EBC SPORT ኢቢሲ ስፖርት's post 02/06/2026

የጋና ብሄራዊ ቡድን የዓለም ዋንጫ ስብስቡን ይፋ አደረገ
***********

በ2026ቱ የዓለም ዋንጫ ጥቋቁር ክዋክብቱን የጋና ብሄራዊ ቡድን የሚወክሉ አባላት ይፋ ሲሆኑ፤ ሀያ ስድስት ተጫዋቾች ተካተዋል።

በፖርቹጋላዊው አሰልጣኝ ካርሎስ ኬሮዥ የሚመራው የጋና ብሄራዊ ቡድን ዛሬ ካርዲፍ ላይ ከዌልስ ብሄራዊ ቡድን ጋር የወዳጅነት ጨዋታ ያደርጋል። ከዚህ ጨዋታ በኋላ ወደ ሰሜን አሜሪካ ያመራል።

እናም በዚህ ስብስብ ከተካተቱት መሀል የቀድሞ የአርሰናል ኮከብ የቪያሪያሉ ቶማስ ፓርቴይ እና የማንቸስተር ሲቲው አንቶይን ሴሜኒዮ በስብስቡ ከተካተቱት ተጫዋቾች መሀል ናቸው።

የሌስተር ሲቲው አንጋፋ አጥቂ ጆርዳን አዪው ቡድኑን በአምበልነት የሚመራው ሲሆን፤ የቶተንሀሙ ሙሀመድ ቁዱስ በጉዳት ከስብስቡ ውጪ እንደሚሆን ተገልጿል።

የጋና ብሄራዊ ቡድን ከእንግሊዝ፣ ክሮሺያ እና ፓናማ ጋር በምድብ 11 ተደልድሏል።

በእድሪስ አህመድ

Photos from EBC SPORT ኢቢሲ ስፖርት's post 02/06/2026

አሰልጣኝ ማርኮ ሲልቫ ቤኒፊካን ለመረከብ ተቃርቧል
**************

የፉልሃሙ አሰልጣኝ ማርኮ ሲልቫ የፖርቹጋሉን ክለብ ቤኒፊካን በኃላፊነት ለመረከብ ተቃርቧል።

የ48 ዓመቱ ፖርቹጋላዊ አሰልጣኝ በቅርብ ቀናት ውስጥ ከተደረጉ ስኬታማ ንግግሮች በኋላ ከቤኒፊካ ጋር ስምምነት ላይ ለመድረስ መቃረቡን ቢቢሲ ስፖርት ዘግቧል።

ሲልቫ ከፉልሃም ጋር ያለው ውል በዚህ ወር የሚጠናቀቅ ሲሆን፣ ምንም እንኳን የፕሪሚየር ሊጉ ክለብ አዲስ ውል ቢያቀርብለትም እስካሁን ጥያቄውን አልተቀበለውም።

ቤኒፊካ ጆዜ ሞሪንሆ የሪያል ማድሪድ ዋና አሰልጣኝ ለመሆን ክለቡን ለቀው መውጣታቸውን ተከትሎ ተተኪ አሰልጣኝ በመፈለግ ላይ ይገኛል።

ሲልቫ በ2021 ፉልሃምን ተረክቦ በመጀመሪያው የውድድር ዘመን ክለቡ ወደ ፕሪሚየር ሊግ እንዲያድግ አድርጓል።

እስካሁን ይፋዊ መግለጫ ያልተሰጠ ቢሆንም፣ ማርኮ ሲልቫ ከቤኒፊካ ጋር ወደ ፖርቹጋል እግር ኳስ የመመለስ ዕድሉ በከፍተኛ ሁኔታ የሰፋ ይመስላል።

በእሱባለው ተሾመ

Photos from EBC SPORT ኢቢሲ ስፖርት's post 02/06/2026

ቴክቦል (Teqball)፦ አዲሱና አስደሳች የኳስ ስፖርት
*****************

ቴክቦል የእግር ኳስ ክህሎትን ከጠረጴዛ ቴኒስ ሕግጋት ጋር አጣምሮ የያዘ፣ ኳሱ በእጅ ሳይነካ በታጠፈ ጠረጴዛ ላይ የሚጫወቱት አስደሳች ስፖርት ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት በመላው ዓለም ተወዳጅነትን እያገኘ ይገኛል።

ይህ ስፖርት ለመጀመሪያ ጊዜ እ.አ.አ በ2012 በሃንጋሪ የተጀመረ ሲሆን፣ ጋቦር ቦርሳኒ፣ ቪክቶር ሁሳር እና ጂዮርጂ ጋትያን በተባሉ ሦስት ግለሰቦች አማካኝነት ወደ ሥራ ገብቷል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዛሬው ዕለት በይፋ ያስመረቁት ከእንጦጦ እስከ ቀጨኔ መድኃኔዓለም ያለው የመልሶ ማልማት እና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት ይህንን የስፖርት ዓይነት ያካተተ ነው።

የቴክቦል ዋነኛው መለያ ባህሪ "ቴክቦርድ" (Teqboard) ተብሎ የሚጠራውና መሃሉ ከፍ ብሎ ጫፎቹ ወደ ታች የታጠፈ ልዩ ጠረጴዛ መሆኑ ነው። ይህ የጠረጴዛው ቅርጽ ኳሱ በየትኛውም አቅጣጫ እንዲነጥርና ጨዋታው ፍጥነትና ከፍተኛ ክህሎት እንዲኖረው ያደርጋል።

የስፖርቱ ሕጎች በጣም ቀላልና ለማንም ሰው ለመረዳት ምቹ ሲሆኑ፣ በሁለት ተቃራኒ ተጫዋቾች (አንድ ለአንድ) ወይም በቡድን (ሁለት ለሁለት) ሊጫወቱት የሚችሉት ስፖርት ነው።

ልክ እንደ እግር ኳስ ሁሉ፣ ኳሱን በእጅ መንካት በጥብቅ የተከለከለ ሲሆን፤ ተጫዋቾች ኳሱን በጭንቅላታቸው፣ በደረታቸው፣ በትከሻቸው ወይም በእግራቸው መምታት ይችላሉ።

አንድ ተጫዋች ወይም ቡድን ኳሱ ወደ ተቃራኒው ወገን ከመሻገሩ በፊት ቢበዛ ሦስት ጊዜ ብቻ የመንካት መብት አለው።

በአንድ የሰውነት ክፍል (በእግር ብቻ) በተከታታይ ሁለትጊዜ ኳሱን መንካት አይፈቀድም። ይህም ተጫዋቾች የተለያዩ የሰውነት ክፍሎቻቸውን እንዲጠቀሙና የተለየ ብቃት እንዲያሳዩ ያስገድዳቸዋል።

በአሁኑ ወቅት ቴክቦል በዓለም አቀፍ ደረጃ በፌዴሬሽን የሚመራ ሲሆን፣ ወደ ኦሎምፒክ ስፖርቶች እንዲካተትም ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ ይገኛል። እንደ ሮናልዲንሆ ያሉ ታዋቂ የዓለም እግር ኳስ ተጫዋቾች የስፖርቱ አምባሳደር በመሆን እያስተዋወቁት ይገኛሉ።

ስፖርቱ ምንም ዓይነት የአካል ንክኪ ስለሌለውና በትንሽ ቦታ ላይ ሊከናወን ስለሚችል ጉዳትን የሚቀንስ ከመሆኑም በላይ ለተጫዋቾች ትኩረትን፣ ቅልጥፍናን እና የኳስ ቁጥጥርን ለማሻሻል ትልቅ አስተዋጽኦ አለው።

በተጨማሪም የልብ ጤናን የሚያሻሽል፣ አእምሮን የሚያነቃቃ እንዲሁም የአይን፣ የእግር እና የአእምሮ ቅንጅትን በማሳደግ ፈጣን ውሳኔ የመስጠት ብቃትን የሚያዳብር ስፖርት ነው፤ ዕድሜና ጾታ ሳይለይ ሁሉም ሰው ሊጫወተው ስለሚችል፣ የአእምሮ ውጥረትን ለመቀነስና ማኅበራዊ ግንኙነትን ለማጠናከር ከፍተኛ ጠቀሜታ አለው።

በዘረንቶስ ሰለሞን

Ethiopian Broadcasting Corporation

02/06/2026

ሊቨርፑል አንዶኒ ኢራኦላን የክለቡ አሰልጣኝ አድርጎ ለመሾም ተስማማ
*****************

የመርሲሳይዱ ክለብ ሊቨርፑል፣ ስፔናዊውን አንዶኒ ኢራኦላን አዲሱ የክለቡ አሰልጣኝ አድርጎ ለመሾም የመጨረሻው ስምምነት ላይ መድረሱን ፋብሪዚዮ ሮማኖ ዘግቧል።

የ43 ዓመቱ አሰልጣኝ በበኩላቸው ወደ አንፊልድ በማምራት የሊቨርፑልን ኃላፊነት ለመረከብ ትልቅ ፍላጎት እንዳላቸው አሳይተዋል።

ይህንን የቅጥር ሂደት በበላይነት እየመሩት የሚገኙት የክለቡ ስፖርቲንግ ዳይሬክተር ሪቻርድ ሂውዝ ሲሆኑ፣ ድርድሩም በስኬት መጠናቀቁ ተሰምቷል።

በዘረንቶስ ሰለሞን

Photos from EBC SPORT ኢቢሲ ስፖርት's post 02/06/2026

የዓለም አትሌቲክስ የዮሚፍ ቀጄልቻ እና የሳሮን በርሄን የዓለም ክብረ ወሰኖች አፀደቀ
*******************

የካቲት ወር 2025 ላይ በካስቴሎን የ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ውድድር አትሌት ዮሚፍ ቀጄልቻ ሲያሸንፍ ያስመዘገበው 26 ደቂቃ ከ31 ሰከንድ ፣ የወንዶች የ10 ኪሎ ሜትር የዓለም ክብረወሰን ሆኖ ተመዝግቧል።

ክብረወሰኑ ሊጸድቅ የቻለው ቀደም ሲል ኬንያዊው አትሌት ሮኔክስ ኪፕሩቶ አስመዝግቦት የነበረው የ26 ደቂቃ ከ24 ሰከንድ ውጤት ፣ በአበረታች ቅመም (ዶፒንግ) ህግ ጥሰት ምክንያት ሙሉ በሙሉ በመሰረዙ ነው።

በዚህ መሠረት የሁለት ጊዜ የዓለም የ10 ሺህ ሜትር የብር ሜዳሊያ ባለቤቱ ዮሚፍ ቀጄልቻ፣ በቫሌንሲያ ያስመዘገበውን የግማሽ ማራቶን የዓለም ክብረወሰንን ጨምሮ በአንድ ጊዜ የሁለት ክብረወሰኖች ባለቤት ሆኗል።

አትሌት ዮሚፍ ከሳምንታት በፊት በለንደን ማራቶን ከሁለት ሰዓት በታች በመግባት ከሴባስቲያን ሳዌ አዲስ የማራቶን ክብረወሰን መስበሩ አይዘነጋም።

በሌላ በኩል አትሌት ሳሮን በርሄ በኦስትራቫ የካቲት ወር 2026 ላይ በ1500 ሜትር ያስመዘገበችው የ4 ደቂቃ ከ 01:23 ሰከንድ ሰዓት የዓለም ከ20 ዓመት በታች አዲስ ክብረወሰን ሆኖ በይፋ ጸድቋል።

ከኢትዮጵያዊያኑ በተጨማሪ የሌሎች አራት አትሌቶች ክብረወሰንም በይፋ እውቅና አግኝቷል።

በአዲስ የሺዋስ

Photos from EBC SPORT ኢቢሲ ስፖርት's post 02/06/2026

ቼልሲ ለአቺምፖንግ የቀረቡለትን ጥያቄዎች ውድቅ አደረገ
******************

ቼልሲ ለወጣቱ ተከላካይ ጆሽ አቺምፖንግ የቀረቡለትን በርካታ የዝውውር ጥያቄዎች ውድቅ ማድረጉን ቢቢሲ ስፖርት ዘግቧል።

የክለቡ የአካዳሚ ውጤት የሆነው የ20 ዓመቱ ተጫዋች በክለቡ ውስጥ እንደ ኮል ፓልመር፣ ጆአኦ ፔድሮ እና ሞይስ ካይሴዶ የማይነካ ተጫዋች ሲሆን፣ የቼልሲ የወደፊት ዕቅዶች ዋነኛ አካል ተደርጎም ይታያል።

​ባለፈው የውድድር ዘመን በፕሪሚየር ሊጉ ያደረገው ጨዋታ 17 ብቻ ቢሆንም፣ ቼልሲ ይህንን የእንግሊዝ ከ21 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ተጫዋች በስታምፎርድ ብሪጅ ለማቆየት ቁርጠኛ መሆኑ ተሰምቷል።

አርሰናል፣ ኒውካስል ዩናይትድ፣ ክሪስታል ፓላስ እና ቦርንማውዝን ጨምሮ በርካታ የፕሪሚየር ሊግ ክለቦች የተጫዋቹን ሁኔታ በቅርበት እየተከታተሉ ይገኛሉ፤ ይሁን እንጂ ቼልሲ ወጣቱን ተከላካይ ለመሸጥ ምንም ዓይነት ፍላጎት እንደሌለው በግልጽ አስታውቋል።

​በስምንት ዓመቱ ቼልሲን የተቀላቀለው አቺምፖንግ፣ በክለቡ እስከ 2029 ድረስ የሚቆይ ውል አለው።

በእሱባለው ተሾመ

Photos from EBC SPORT ኢቢሲ ስፖርት's post 02/06/2026

የአርሰናል የቀጣዩ የውድድር ዘመን ዕቅድ
****************

አርሰናል ለ22 ዓመታት የቆየውን የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫ ካሳካ በኋላ ከወዲሁ ለቀጣዩ የውድድር ዘመን እያቀደ ነው።

​የቢቢሲ ስፖርት ዘገባ እንደሚያመለክተው መድፈኞቹ በአሰልጣኝ ሚኬል አርቴታ እየተመሩ በክረምቱ ታላቅ የቡድን ግንባታ ለማድረግ እየተዘጋጁ ይገኛሉ።

የክለቡ ቀዳሚው ስራ የአርቴታን ውል ማራዘም ሲሆን፥ በሚቀጥሉት ሳምንታት ውስጥ በአዲሱ ውል ጉዳይ ከስፔናዊው አሰልጣኝ ጋር ንግግር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል።

​በዝውውር ገበያው ላይ አርሰናል በርካታ የአጥቂ መስመር ተጫዋቾችን ኢላማ አድርጓል።

የአስቶን ቪላው ኮከብ ሞርጋን ሮጀርስ፣ የቦርንማውዙ ድንቅ ታዳጊ ኤሊ ጁኒየር ክሩፒ እና የአትሌቲኮ ማድሪዱ አጥቂ ጁሊያን አልቫሬዝ በክለቡ የእጩዎች ዝርዝር ውስጥ ይገኛሉ።

ሮጀርስ እና ክሩፒ እያንዳንዳቸው ከ80 ሚሊዮን ፓውንድ በላይ ሊያስወጡ የሚችሉ ሲሆን፣ አልቫሬዝ ደግሞ ከ120 ሚሊዮን ፓውንድ በላይ የዋጋ ተመን እንደተቀመጠበት ተዘግቧል።

​አዳዲስ ለሚመጡ ተጫዋቾች የሚሆን የፋይናንስ አቅም ለመፍጠር አርሰናል ጋብርኤል ጄሱስ፣ ጋብርኤል ማርቲኔሊ፣ ሊያንድሮ ትሮሳርድ፣ ቤን ዋይት፣ ፋቢኦ ቪዬራ እና ሪስ ኔልሰንን ጨምሮ ለበርካታ ተጫዋቾች የሚቀርቡ የዝውውር ጥያቄዎችን ለመመልከት አስቧል።

​ክለቡ በተጨማሪም የአማካይ እና የተከላካይ መስመሩን ለማጠናከር እያሰበ ይገኛል፤ ለዴክላን ራይስ እና ለዩሪየን ቲምበርም አዲስ ውል እንደሚያቀርብ ይጠበቃል።

​የፕሪሚየር ሊጉን ዋንጫ ካነሳ በኋላ አርሰናል አሁን ላይ ትኩረቱን ያደረገው በቀጣዩ የውድድር ዘመን በእንግሊዝም ሆነ በአውሮፓ የበላይነትን መያዝ የሚችል ጠንካራ ስብስብ በመገንባት ላይ ነው።

በእሱባለው ተሾመ

Photos from EBC SPORT ኢቢሲ ስፖርት's post 01/06/2026

በሪያል ማድሪድ የሚፈለገው ሮድሪ
*************

‎በማንቸስተር ሲቲ ቤት የአንድ ዓመት ቀሪ ኮንትራት ያለው ሮድሪ ከዓለም ዋንጫ በኋላ ስለ ቆይታው ጉዳይ እንደሚያሳውቅ ተናግሯል።

‎የፕሬዚዳንት ፍሎሬንቲኖ ፔሬዝ ተፎካካሪ ሆነው የቀረቡት ዕጩ ተወዳዳሪ ኤነሪኬ ሪኩዌልሜ ከተመረጡ ሮድሪን ወደ ማድሪድ መውሰድ ይፈልጋሉ።

‎ስለ ጉዳዩ የተጠየቀው ሮድሪ "አሁን ኃላፊነቴ የዓለም ዋንጫ ላይ ማተኮር ነው እኔን የሚመለከቱ ጉዳዮች ከዓለም ዋንጫው በኋላ ይደረሳሉ" ብሏል።

‎በነፃነት ጫንያለው

Want your business to be the top-listed Gym/sports Facility in Addis Ababa?

Click here to claim your Sponsored Listing.

Location

Category

Telephone

Address


Addis Ababa
3344