16/04/2026
🚨ሊዮኔል ሜሲ የክለብ ባለቤት ሆኗል !
አርጀንቲናዊው ኮከብ ሊዮኔል ሜሲ በስፔን ሦስተኛ ዲቪዚዮን እየተወዳደረ የሚገኘውን ኮርኔላን ክለብ መግዛቱ ይፋ ሆኗል። ጥበበኛው ኮከብ በካታሎኒያ የሚገኘውን ክለብ ሙሉ ለሙሉ በባለቤትነት እንደሚያስተዳድርም ታውቋል።
ፖርቹጋላዊው ኮከብ ክርስቲያኖ ሮናልዶ በቅርቡ ስፔን ላሊጋ 2 ጠንካራ ተፎካካሪ የሆነውን ክለብ ዩዲ አልሜሪያ 25 በመቶ የባለቤትነት ድርሻ በመግዛት እንደ ዴቪድ ቤካም እና ሮናልዶ ናዛሪዮ ያሉ ታዋቂ ተጫዋቾችን ፈለግ መከተሉ ይታወቃል።
15/04/2026
"በርበሬዎቹ" ፕሪሚየርሊጉን ተቀላቀሉ!
: በሀዋሳ አርቴፊሻል ሜዳ ሲካሄድ በቆየው የከፍተኛ ሊግ ምድብ “ለ” ፉክክር ወደ ፕሪሚየርሊጉ ያደገው ክለብ ታውቋል። ዛሬ በ19ኛ ሳምንት በአንድ ነጥብ ልዩነት የሚከተለውን ደሴ ከተማን 1 ለ 0 ማሸነፍ የቻለው ሀላባ ከተማ አንድ ጨዋታ እየቀረው በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ 2019 ዓም የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አድጓል። ወሳኟን ጎልም እስራኤል ሸጎሌ አስቆጥሯል።
ባለፈው ሳምንት በ18ኛው ሳምንት የምድቡ መሪ ሀላባ ከተማ ከሶሎዳ ዓድዋ ጋር 0ለ0 በመለያየቱ ወሳኝ ነጥብ ጥሏል። በአንፃሩ ደሴ ከተማ አዲስ አበባ ከተማን 2ለ1 ማሸነፉን ተከትሎ ከመሪው ሀላባ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አንድ ብቻ ማጥበብ ችሏል። ይህም ሁለቱ ክለቦች ትናንት በ19ኛ ሳምንት መርሀግብር እርስበርስ በመገናኘታቸው ፉክክሩን ይበልጥ ልብ አንጠልጣይ አድርጎት ነበር።
በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ምስረታቸው ረዘም ካሉት ክለቦች መካከል አንዱ የሆነው ሀላባ ከተማ እግር ኳስ ክለብ በኢትዮጵያ እግርኳስ ከ60 ዓመታት ገደማ እድሜ ቢኖረውም ለኢትዮጵያ እግር ኳስ በርካታ ተጫዋቾችን ከማበርከት ባለፈ በትልቁ ሊግ ላይ ሳንመለከተው ቆይተናል፡፡ በተለያዩ ውድድር ዘመናትም ወደ ፕሪሚየርሊግ ለማደግ ከፍተኛ ፉክክር አድርጎ በመጨረሻ ሳምንታት የማለፍ እድሉን አሳልፎ ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ "በርበሬዎቹ" በሚል ቅፅል ስም የሚታወቀው ሀላባ ከተማ ዘንድሮ ግን በበሽር አብደላ እየተመሩ ሊጉን ለመቀላቀል በቅተዋል። ክለቡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ መዋቅር ውስጥ በተለያዩ እርከኖች ሲወዳደር የቆየ ቢሆንም፣ ወደ ከፍተኛ ሊጉ (ሁለተኛው እርከን) ያደገውና በቋሚነት መወዳደር የጀመረው ከ2007 ዓ.ም ጀምሮ ነው። በኢትዮጵያ እግር ኳስ ብዙ አሻራ ያሳረፈው ደሴ ከተማ (ቅኝቶቹ) ዘንድሮም ህልሙ እውን ሊሆን አልቻለም።
በዘንድሮው የከፍተኛ ሊግ ፉክክር ከምድብ “ሀ” ጋሞ ጨንቻ በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የ2019 ዓም የኢትዮጵያ ፕሪሚየርሊግ ተፎካካሪ መሆኑን ከቀናት በፊት ማረጋገጡ ይታወቃል፡፡ ጋሞ ጨንቻና ሀላባ ከተማ የከፍተኛ ሊጉን ዋንጫ ለማንሳት በቀጣይ የሚፋለሙ ይሆናል፡፡
14/04/2026
የባርሳ ሰራዊት: የ2017ቱን ታሪካዊ ምሽት ፍለጋ!
: በቻምፒዮንስሊግ ታሪክ መጋቢት 8 ቀን 2017 የማይረሳ ምሽት ነው። ትልቁ የቻምፒዮንስሊግ መድረክ በታሪክ ከማይዘነጋቸው አንዱ የውጤት ቅልበሳ የታየው በዚያ ምሽት ነበር። በዚያች ተአምራዊ ምሽት በካምፕ ኑ ሰርጂዮ ሮቤርቶ ወሳኟን 6ኛ ጎል ለባርሴሎና ከመረብ ሲያሳርፍ የነበረውን ሁኔታ ማንም ሊዘነጋው አይችልም። በካምፕ ኑ ጨዋታውን ለመመልከት የታደሙ 96ሺ ተመልካቾች አቅላቸውን የሳቱበት፣ የካታላኗ ከተማ መሬት የተንቀጠቀጠበት ምሽት!
ከ9 ዓመት በፊት ባርሴሎና በቻምፒዮንስሊግ ሩብ ፍፃሜ የመልስ ጨዋታ ከፓሪስ ሴን ዠርማ ጋር የተገናኘበት ታሪካዊ ጨዋታ፣ ካታሎኒያዊያኑ ከፈረንሳይ ዋና ከተማ ሲመለሱ ሁሉ ነገር እንዳበቃለት አስበዋል። በፔዤ 4-0 የተረመረሙበት ጨዋታ ተአምራዊ ተደርጎ ታይቷል። ለፓሪሱ ክለብ በካታር ስፖርትስ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ከተጠቀለለ በኋላ የተመዘገበ ድንቅ ውጤት ነበር።
በወቅቱ የባርሴሎና ህዝብ ግንኙነት ሀላፊነት የነበሩት ሆዜ ማኑኤል ላዛሮ ከሽንፈቱ በኋላ የነበሩት ጥቂት ቀናት ጭፍግግ ያሉ እንደነበሩ ያስታውሳሉ። “ከቻምፒየንስ ሊግ እንደተሰናበትን አሰብን። ቀናት አለፉ። ሳምንታት ተተኩ። አትሌቲኮን 2-1 አሸነፍን፣ ስፖርቲንግ ሂዮንን 6-1 ረመረምን። ከፔዤ ጋር የምናከናውነው የመልስ ጨዋታ አራት ቀናት ሲቀረው ሴልታ ቪጎን 5-0 አሸነፍን። በሁላችንም ዘንድ ጨዋታው አላበቃም የሚል ስሜት ተፈጠረ። ልዊስ ኤንሪኬ(በወቅቱ የባርሳ አሰልጣኝ ነበር) ተስፋ መቁረጥ የሚባል ነገር የሚያውቅ ሰው አልነበረም” ይላሉ።
ኤንሪኬ በአሰልጣኝ ቡድኑ የስነ ልቦና ባለሞያ ነበረው። ዮአኪን ቫልዴዝ ይባላሉ። ለቡድኑ ትልቅና የማይናቅ ሚና አላቸው። ባርሳ በመጀመሪያው ጨዋታ በደረሰበት ሽንፈት ደጋፊዎቹ ተስፋ ሳይቆርጡ በመልሱ ጨዋታ ካምፕ ኑ ስቴድየምን ሞልተውታል። “yes we can” እና “we will complete the come back” የሚሉ ባነሮችን ይዘው ቦታቸው ላይ ተሰይመዋል።
በጉጉት የሚጠበቀው ጨዋታ ተጀመረ። ባርሳ በልዊስ ሱአሬዝ ጎል ጥሩ አጀማመር አደረገ። ላይቪን ኩርዛዋ ራሱ ላይ ያስቆጠረው ጎል የካታላኑን ክለብ 2-0 መሪ አደረገው። ከእረፍት መልስ ብራዚላዊው የኳስ አርቲስት ኔይማር ላይ ጥፋት ተሰርቶ አርጀንቲናዊው ምትሃተኛ ሊዮኔል ሜሲ የተሰጠውን ፍፁም ቅጣት ምት ቀለል አድርጎ በማስቆጠር የባርሳን መሪነት አሳደገ።
በድንገት ኤዲንሰን ካቫኒ ለፓሪሱ ክለብ ያስቆጠረው ጎል ግን ለባርሳ ሁሉ ነገር እንዳበቃለት እንዲታሰብ አደረገ። 88ኛ ደቂቃ ላይ ኔይማር ጎል አስቆጥሮ የቡድኑን አልሸነፍ ባይነት መንፈስ ወደ ጋለ ስሜት ቀየረው። ከሁለት ደቂቃ በኋላም አስደናቂው ኔይማር ሌላ ግብ ደግሞ የባርሳን የሞተ የቻምፒዮንስሊግ ተስፋ ነብስ ዘራበት። 5 ደቂቃ ተጨመረ።
ባለቀ ሰዓት ባርሳ የቅጣት ምት ኳስ ሲያገኝ ግብ ጠባቂው ማርክ አንድሬ ቴር ስቴገን ሳይቀር ወደ ፊት ሄዶ ኳስ እንዲሻማ ተፈቀደለት። ኳሷ ተመለሰች። ኔይማር ግን ቬራቲን አልፎ ኳሷን አሻገረ። ዤራርድ ፒኬን አለፈችው። ሮቤርቶን ግን አላለፈችውም። ኳስ እና መረብ አገናኘ። ካምፕ ኑ በአንድ እግሩ ቆመ። የማይመስል የሚመስለው ታሪክም በካምፕ ኑ ጀግኖች በወርቅ ቀለም ተፃፈ። እነሆ ቻምፒዮንስሊግም ያንን ምሽት በታሪክ ሲያስታውሰው ይኖራል። ዛሬስ፣ አዲሱ የባርሳ ትውልድ፣ የሀንሲ ፍሊክ ሰራዊት ከሜዳው ውጪ የአትሌቲኮ ማድሪድን ያለፈው ሳምንት የ2ለ0 ውጤት ይቀለብሳል?
14/04/2026
🇵🇹 😮ከአውሮፓ ለየት ካሉ ታዋቂ ስታዲየሞች መካከል አንዱ የፖርቱጋሉ ክለብ ኤስ.ሲ. ብራጋ ስታዲየም ነው። የብራጋ ከተማ ማዘጋጃ ቤት ያስገነባውን ይህን ስታዲየም ዲዛይን ያደረገው አርክቴክት ኤድዋርዶ ሶውቶ ዴ ሞውራ ይባላል። ይህ አርክቴክት የስታዲየሙን ዲዛይን ሲሰራ ስለ እግር ኳስ ምንም የሚያውቀው ነገር እንዳልነበረ አምኗል።
ይህ ልዩ ስታዲየም ሁለት መመልከቻዎች (stands) ብቻ ያሉት ሲሆን፣ በሞንቴ ዶ ካስቶር ተራራ ጎን የተገነባ እና ከቀድሞው የካስትሮ የድንጋይ ማውጫ ተራራ ተፈልፍሎ የተሰራ ነው! 🤯
ስታዲየሙን ለመገንባት በግምት 150 ሚሊዮን ፓውንድ ወጪ የተደረገበት ሲሆን፣ 30,000 ተመልካቾችን ማስተናገድ ይችላል 🏟️
13/04/2026
አስገራሚው የ31 ለ 0 ውጤት!!
🤔 : በኢንተርናሽናል የብሔራዊ ቡድን ጨዋታዎች ታሪክ በርካታ ፍልሚያዎች በሰፊ የግብ ልዩነት ሲጠናቀቁ ታይተዋል። በትልቁ ዓለም ዋንጫ መድረክ ሳይቀር በሰፊ የግብ ልዩነቶች የተጠናቀቁ በርካታ ጨዋታዎች በታሪክ ተመዝግበው ይገኛሉ።
በብሔራዊ ቡድኖች መካከል በተካሄዱ ጨዋታዎችን በሰፊ የግብ ልዩነት የተጠናቀቁ ብሎ ፊፋ ከመዘገባቸው ውጤቶች መካከል አንዱ ከ25 ዓመት በፊት ልክ ከትናንት በስቲያ አፕሪል 11/2001 ነበር የተመዘገበው።
ይህ ታሪካዊ ጨዋታ በአውስትራሊያ 31 ለ 0 ድል የተጠናቀቀ ሲሆን፣ ከባዱ ሽንፈት የደረሰባት ደግሞ በእግር ኳስ ስሟ ሲጠራ የማትታወቀው የኦሽኒያዋ አሜሪካን ሳሞአ ናት። ጨዋታው በኦሽኒያ ሀገራት መካከል ለ2002 የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ የተካሄደ ነበር። በመጀመሪያ የማጣሪያ ጨዋታዋ ቶንጋን 22 ለ 0 ያሸነፈችው አውስትራሊያ፣ በፊጂ 13 ለ 0 የተሸነፈችው ሳሞአ ጋር በኮፍስ ሀርበር ስቴድየም ተገናኙ።
በሦስት ሺ ተመልካቾች ፊት የተካሄደው የአውስትራሊያና ሳሞአ ጨዋታ ገና ከ10ኛው ደቂቃ ጀምሮ ግብ ቢያስተናግድም ታሪክ የማይረሳው ውጤት ይመዘገብበታል ብሎ ያሰበ ግን አልነበረም። የአውስትራሊያው አማካኝ ኮን ቦትሲያኒስ ሀገሩን ገና በጊዜ መሪ አደረገ። ኋላ ላይም በ50ኛው እና 84ኛው ደቂቃ ላይ ባስቆጠራቸው ግቦች ሐትሪክ ሰርቷል።
ታሪካዊ ውጤት በተመዘገበበት ጨዋታ ግን ቀዳሚዋን ግብ ከመረብ አሳርፎ ሐትሪክ ከሰራው ተጫዋች በላይ አርቺ ቶምሰን የተባለውና ሌሎችም የአውስትራሊያ ተጫዋቾች የጨዋታው ኮከብ ነበሩ። ቶምሰን የተባለው ተጫዋች ለማመን በሚከብድ ሁኔታ (12', 23', 27', 29', 33', 37', 42', 45', 56', 60', 65', 85', 88') ደቂቃዎች በጨዋታው አስራ ሶስት ግቦችን በተጋጣሚ መረብ ላይ አዘነበ።
አጥቂው ዴቪድ ዝሪሊችም ብዙ አልራቀም፣ (13', 21', 25', 33', 58', 66', 78', 89') ደቂቃዎች ስምንት ግቦችን ከመረብ አዋህዷል። ሌሎቹን የአውስትራሊያ ግቦች ኦሬሊዮ ቪድማር በ (14', 80') ደቂቃ፣ ቶኒ ፖፖቪች (17', 19') ደቂቃዎች፣ ሳይመን ኮሎሲሞ (51', 81') እና ፉስቶ ደ ኤሚሲስ በ55ኛ ደቂቃ ማስቆጠር ችለዋል።
ይህ የአውስትራሊያ የ31 ለ 0 ድል በብሔራዊ ቡድኖች ኢንተርናሽናል ጨዋታ ሪከርድ ሆኖ ከ25 ዓመት በፊት ቢመዘገብም፣ በአጠቃላይ የእግር ኳስ ታሪክ አፈታሪክ ከሚመስለው የ149 ለ 0 ውጤት ጋር ሲነፃፀር በብዙ ርቆ ይገኛል።
ብዙዎች "የማያምኑት" የ149 ለ 0 ውጤት በእግር ኳስ ታሪክ ትልቁ ተብሎ ይታወቃል። ይህ ውጤት የተመዘገበውም በአፍሪካዊቷ ደሴት 2002 ላይ በማዳጋስካር ሊግ AS Adema የተሰኘ ክለብ S.O. l'Emyrne የተባለውን ክለብ የረታበት መሆኑ በብዙ የመረጃ ምንጮች ተጠቅሶ ይገኛል።🤔
13/04/2026
ጋሞ ጨንቻ- የፕሪሚየር ሊጉ አዲስ እንግዳ !
አጓጊ ፉክክሮችን እያስተናገደ ጫፍ በደረሰው የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ከምድብ ሀ ጋሞ ጨንቻ በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የ2019 ዓም የኢትዮጵያ ፕሪሚየርሊግ ተፎካካሪ መሆኑን አረጋግጧል።
በምድብ ሀ የመጨረሻ ጨዋታ ዛሬ በጅማ ስታዲየም ቡራዩ ክፍለ ከተማን የገጠመው ጋሞ ጨንቻ 3ለ0 ማሸነፉን ተከትሎ ምድቡን በበላይነት በማጠናቀቅ የፕሪሚየር ሊጉን ፉክክር ተቀላቅሏል።
በከፍተኛ ሊጉ አስደናቂ የውድድር ዓመት ያሳለፈው ጋሞ ጨንቻ በ41 ነጥብ በበላይነት ሲያጠናቅቅ አንድ ጊዜ ብቻ ሽንፈት ገጥሞታል። 12 አሸንፎ በ5 ጨዋታ አቻ ሲለያይ በአጠቃላይ በ18 ጨዋታዎች መረቡን ያስደፈረውም ሁለት ጊዜ ብቻ ነው። በ2004 ዓም የተመሰረተው ጋሞ ጨንቻ በ2011 ዓ.ም ወደ ኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ማደጉ ይታወቃል።
በዚሁ በከፍተኛ ሊግ ምድብ ለ በሀዋሳ አርቴፊሻል ሜዳ ወደ ፕሪሚየርሊጉ ለማደግ የሚደረገው ፉክክር እጅግ አጓጊ ሆኖ ቀጥሏል። በ19ኛው ሳምንት የምድቡ መሪ ሀላባ ከተማ ከሶሎዳ ዓድዋ ጋር 0ለ0 በመለያየቱ ወሳኝ ነጥብ ጥሏል። በአንፃሩ ደሴ ከተማ አዲስ አበባ ከተማን 2ለ1 በማሸነፍ ከመሪው ሀላባ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አንድ ብቻ ማጥበብ ችሏል። ሀላባ ከተማ እና ደሴ ከተማ ወደ 2019 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ለማለፍ የሚያደርጉት ፉክክር እስከ መጨረሻው ሳምንት ድረስ አጓጊ ሆኖ ይቀጥላል።
12/04/2026
🔥 ታሪክ ሰሪው ምስጋና ዋቁማ!🙏
🥈🇪🇹💪በፓሪስ ኦሊምፒክ የ20 ኪሜ ውድድር ባሳየው አስደናቂ ብቃት የብዙዎችን ትኩረት የሳበው አትሌት ምስጋና ዋቁማ፣ በኢትዮጵያ የርምጃ ውድድር ታሪክ "ማርሽ" እየቀየረ ይገኛል።
በቅርቡ በተካሄደው የኢትዮጵያ ቻምፒዮና በራሱ ተይዞ የነበረውን የ10 ኪሜ ሪከርድ ያሻሻለው ምስጋና በፓሪስ ኦሊምፒክ 1:19:31 በሆነ ሰዓት 6ኛ ደረጃን ይዞ በማጠናቀቅ የከፈተውን የድል በር ዛሬ ብራዚሊያ ላይ ቀጥሎታል።
ምስጋና ዋቁማ ዛሬ በብራዚል ዋና ከተማ ብራዚሊያ በተካሄደው የዓለም አትሌቲክስ የርምጃ የቡድን ቻምፒዮና ላይ በወንዶች ግማሽ ማራቶን ተፋልሞ በኢትዮጵያ የርምጃ ውድድሮች ታሪክ የመጀመሪያውን ዓለም አቀፍ የብር ሜዳልያ በማጥለቅ ትልቅ ታሪክ ሰርቷል።
ጣሊያናዊው አትሌት ፍራንቸስኮ ፎርቱናቶ በ1፡27፡25 በማጠናቀቅ ባሸነፈበት ውድድር ምስጋና ዋኩማ እስከ መጨረሻ ተፋልሞ በ1፡27፡33 ሁለተኛ በመውጣት፣ ለአፍሪካ አትሌቶች ጭምር በቻምፒዮናው ታሪክ ትልቁን ውጤት አስመዝግቧል።የብራዚሉ ካዮ ቦንፊም በ1፡27፡36 ሶስተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል።ጃፓን የቡድን ዋንጫውን ስታሸንፍ፣ ስፔን እና ቻይና እንደ ቅደም ተከተላቸው የብር እና የነሐስ ሜዳሊያ አግኝተዋል።🙏🙏
12/04/2026
😳🌊 እ.ኤ.አ. በ2004 በተከሰተው አሰቃቂው የሱናሚ አደጋ፣ ማርቱኒስ የተባለ አንድ ትንሽ ልጅ በህይወት ተርፎ ከ10 ቀን በኋላ መገኘቱ መነጋገሪያ ሆኖ ነበር። 😢 በውቅያኖስ ላይ በተንሳፈፉ የእንጨት እና የቤት ስብርባሪዎች ላይ በመንጠልጠል አስፈሪውን ማዕበል ተቋቁሞ በህይወት መትረፍ ቻሀ፣ለ። 🌊
ከብዙ ፍለጋ በኋላ በነብስ አድን ሰራተኞች ሲያገኙት የፖርቹጋል ብሄራዊ ቡድን ማሊያን ለብሶ ነበር 🇵🇹 — ይህ አጋጣሚ ደግሞ የክርስቲያኖ ሮናልዶን ልብ ክፉኛ ነካው ❤️። ከዚያን አስጨናቂ ቀን ጀምሮ ሮናልዶ ማርቱኒስን እንደ ራሱ ቤተሰብ አቅፎና ደግፎ የሚያስፈልገውን ሁሉ ማድረግ ጀመረ።
ዛሬ ላይ ያ ሞትን በጀግንነት ያሸነፈው ልጅ ማርቱኒስ አድጓል፣ ትዳር መስርቷል፣ እንዲሁም የልጅነት የኳስ ተጫዋችነት ህልሙን ተከትሎ ጥረቱን ቀጥልሏ! ⚽️🔥።